ለሦስት ነገሮች ዉዱእ ማድረግ ግዴታ ነው።
1. ለማንኛውም ሶላት
ግዴታም ሆነ ሱና -ለጀናዛ ሶላት እንኳን- ዉዱእ ማድረግ ግዴታ ነው። ምክንያቱም አላህ እንዲህ ይላል፦
“እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ወደ ሶላት በቆማችሁ (ለመቆም ባሰባችሁ) ጊዜ ፊቶቻችሁን፣ እጆቻችሁንም እስከ ክርኖች እጠቡ።” (አል ማኢዳ፤ 6)
ለሶላት መቆም ከፈለጋችሁ እና ዉዱእ የፈታችሁ ከሆነ ታጠቡ ማለቱ ነው።
በተጨማሪም የአላህ መልእክተኛ (ሰ.ዐ.ወ) እንዲህ ብለዋል፦
لا يقبل الله صلاة بغير طهور ، ولا صدقة من غلول
“አላህ ያለ ንፅህና የተሰገደን ሶላት እና ከግዳይ (ምርኮ) ከተሰረቀ ገንዘብ የተለገሰን ምፅዋት አይቀበልም።” (ከቡኻሪይ ውጪ ጀመዓዎች ዘግበውታል)
2. በአላህ ቤት ላይ ለመዞር (ጠዋፍ ለማድረግ)
ኢብኑ ዐባስ እንደዘገቡት የአላህ ነብይ (ሰ.ዐ.ወ) እንዲህ ብለዋል፦
الطواف صلاة إلا أن الله تعالى أحل فيه الكلام ، فمن تكلم فلا يتكلم إلا بخير
“አላህ በውስጡ ንግግርን ፈቅዷል እንጂ ጠዋፍ ሶላት ነው። (በጠዋፍ መሀል) የተናገረም ሰው መልካምን እንጂ አይናገር።” (ቲርሙዚይ እና ዳረቁጥኒይ ዘግበውታል። አል-ሐኪም ሶሒህ ነው ብለውታል። ኢብኑስ-ሰከን እና ኢብኑ ኹዘይማም እንዲሁ)
3. ሙስሐፍን (ቁርአንን) መንካት
አቡበክር ቢን ሙሐመድ ዐምር ቢን ሐዝም ከአባታቸው፣ ከአያታቸው እንደዘገቡት፦ “የአላህ ነብይ (ሰ.ዐ.ወ) ለየመን ሰዎች ደብዳቤ ፃፉ። በውስጡ እንዲህ የሚል ነበረው፦
لا يمس القرآن إلا طاهر
“ንፁህ የሆነ ሰው እንጂ ቁርአንን አይነካም።” (ነሳዒይ፣ ዳረቁጥኒይ፣ በይሃቂይ እና አል-አስረም ዘግበውታል)
ኢብኑ አብደል በር-ር ስለዚህ ሐዲስ ሲናገሩ እንዲህ ይላሉ፦ “ይህ ሐዲስ ተዋቱር (የተደጋገመ ዘገባ) በመሆን የሚመሰል ነው። ምክንያቱም ሰዎች በእጅጉ ተቀብለውታል።”