ሁለተኛው የሐበሻ ስደት
ኢብኑ ሰዕድ እንዲህ ይላሉ፡- “…ከመጀመሪያዋ ስደት ወደ መካ ሲመለሱ ህዝቦቻቸው ይበልጥ ጠነከሩባቸው። ቤተሰቦቻቸው አየሉባቸው። ታላላቅ ግፎችንም አዘነቡባቸው። ከዚያም ተመልሰው ወደ ሐበሻ እንዲሰደዱ መልእክተኛው አዘዙ። ይህኛው ስደት ከመጀመሪያው የከፋ ነበር። ከቁረይሾች በኩል መጠነሰፊ ፈተናዎች ገጥመዋቸዋል።
ቁረይሾች ነጃሺይ ለስደተኞቹ ስላደረገው ጥበቃ ሰምተው ነደዋል። ዑስማን ኢብኑ ዐፋን ‘የአላህ መልእክተኛ ሆይ! በመጀመሪያዋ ስደታችን ላይ አብረውን አልነበሩም። አሁንም ዳግመኛ ስንሰደድ አብረውን አይሄዱም?!’ አሉ። መልእክተኛውም ‘እናንተ ወደ አላህና ወደ እኔ የምትሰደዱ ሰዎች ናችሁ! እነዚህ ሁለት ስደቶች በሙሉ ለናንተ አላችሁ!’ አሉ። ‘የአላህ መልእክተኛ ሆይ! ይህማ ይበቃናል!’ አሉ፤ ዑስማን።”
ከዚያም ወደ ሐበሻ ዳግመኛ ተሰደዱ። የቀድሞው ስደት ላይ ከነበሩት ውጪ ብዙ አዳዲስ ስደተኞች ተጨምረዋል። ቁጥራቸውም -ኢብኑ ኢስሐቅና ሌሎችም እንዳሉት- የወንዶቹ ሰማንያ ሦስት ነበር። ይህ ዓምማር ኢብኑ ያሲር ከነርሱ ጋር ነበረ ካልን ነው። ዓምማርን ካልቆጠርነው ቁጥራቸው ሰማኒያ ሁለት ይሆናል ማለት ነው። ትክክለኛው ይህ ቁጥር ነው ይላሉ፤ ሼኽ አስ-ሱሀይሊይ። ኢማም አልዋቂዲይ፣ ኢብኑ ዑቅባህ እና ሌሎቹም ይህን ይደግፋሉ። ሴቶቹ ደግሞ አስራ ስምንት ነበሩ። አስራ አንዱ የቁረይሽ ጎሳ አባላት ናቸው። ሰባቱ ደግሞ ቁረይሾች አይደሉም። ይህ ቁጥር አብረዋቸው የተሰደዱና እዚያው ሐበሻ ውስጥ የተወለዱ ህጻናቶችን አያካትትም።
ቁረይሾች ስደተኞቹን ለመመለስ ያደረጉት ጥረት
የቁረይሽ አለቆች ሐበሻ ውስጥ ስደተኞቹ በአማን መኖራቸውን፣ መረጋጋታቸውን፣ መኖሪያ መመስረታቸውን፣ አላህን ያለከልካይ ማምለክ መጀመራቸውንና የነጃሺን አቀባበል ሲመለከቱ ምክር ጀመሩ። በስብሰባቸውም ነጃሺይ ስደተኞቹን ወደ ሐገራቸው እንዲመልስ የዲፕሎማሲ ሥራ መስራት እንዳለባቸው ተስማሙ። ይህን ለማሳካት ሙስሊሞችን ከንጉሱ የሚነጥል ዘዴ ማሰብ ጀመሩ። ነገር ግን ይህን የዲፕሎማሲ ጥረት ለማድረግ የተላከው ልኡክ ሳያስበው ኢስላምን ጠቀመ። ልዑኩ ከጠነሰሰው ሴራ በመነሳት በስደተኞቹ መሪ በጃዕፈርና በንጉሱ መሀል የተካሄደው ውይይት የነጃሺን መስለም በማብሰር ተጠናቀቀ። ከዚያም ንጉሱ የስደተኞቹን ደህንነት በእንክብካቤና በጥንቃቄ ለመያዝ ክቡድ ቃል ኪዳኑን ገባ።
የነብዩ ባለቤት የሆኑት ኡሙ ሰለማ ቢንት አቢ ኡመያህ ቢን አልሙጊራህን ዋቢ በማድረግ በተዘገበ ሐዲስ ላይ እንዲህ ሲሉ እናገኛቸዋለን፡-
“የሐበሻን ምድር እንደረገጥን ምርጥ ጠባቂው (ነጃሺ) ዘንድ አረፍን። በኃይማኖታችን ሰበብ ከሚቃጣብን መከራ ዳንን። ያለችግር አላህን ማምለክ ጀመርን። የሚያስከፋንን ነገር እንኳን አልሰማንም። ቁረይሾች ደግሞ ይህን ሲሰሙ በኛ ጉዳይ ላይ ተማከሩ። ኋላም ሁለት ጠንካራ የሆኑ መልእክተኞችንና መካ ውስጥ አለ የሚባልን ስጦታ በሙሉ አስጭነው ሊልኩ ተስማሙ። ነጃሺ ሊወዷቸው ይችላል ያሏቸውን በጊዜው መካ ውስጥ ውድ የሚባሉ የቆዳ ምርቶችን ሰበሰቡ። ከአማካሪዎቻቸውና ቀሳውስቶች መሀል አንዱንም ሳያስቀሩ ለሁሉም ስጦታ ያዙ። ለዚህ ተልእኮም ዐብዱላህ ኢብኑ አቢ ረቢዐህ ቢን አልሙጊራህ አልመኽዙሚይንና ዐምር ቢን አልዐሲ ቢን ዋኢል አስ-ሰህሚይን አምባሳደር አደረጓቸው። ‘ነጃሺን ከማናገራችሁ በፊት ለእያንዳንዱ አማካሪ ስጦታውን እንድትሰጡ! ከዚያም ለነጃሺይ ስጦታውን ስጡት። ከዚያም ስደተኞቹን ሳያወያይ እንዲመልስላችሁ ጠይቁት።’ ብለው አዘዟቸው።”
ኡሙ ሰለማህ ቀጥለዋል…
“መልእክተኞቹ ወደ ነጃሺይ ሐገር ደረሱ። እንደተባሉት አደረጉ። እያንዳንዱን አማካሪ በመንገድ ላይ ሲያገኙት ስጦታውን ይሰጡታል። ነጃሺን ከማናገራቸው በፊት ስጦታውን አዳርሰው ጨረሱ። ለቀሳውስቶቹ እንዲህ አሏቸው። ‘ኃይማኖታቸውን ክደው ከመካ ወደናንተ ሀገር የመጡ ቂል ወጣቶች አሉ። የጎሳዎቻቸውን ኃይማኖት ትተዋል። ወደናንተ ኃይማኖትም አልገቡም። እኛም ሆንን እናንተ የማታውቁት አዲስ ኃይማኖት አምጥተዋል። ታላላቅ የመካ አለቆች እነዚህን ጅሎች ወደ መካ እንድንመልስ ልከውናል። ንጉሱን በነርሱ ጉዳይ ላይ ስናናግረው እንዲያስረክበን ምከሩልን። እንዳያናግራቸውም አድርጉልን። የጎሳ አለቆቻቸውና ህዝቦቻቸው ስለርሱ ይበልጥ ያውቃሉ። ነውራቸውንም ይረዳሉ።’
ቀሳውስቱም ተስማሙ። ከዚያም ለነጃሺ ስጦታቸውን አቀረቡ። ተቀበለ። ከዚያም እንዲህ ሲሉ ጉዳያቸውን አቀረቡ። ‘ንጉስ ሆይ! ኃይማኖታቸውን ክደው ከመካ ወዳንተ ሀገር የመጡ ቂል ወጣቶች አሉ። የጎሳዎቻቸውን ኃይማኖት ትተዋል። ወዳንተ ኃይማኖት አልገቡም። እኛም ሆንን እንተ የማናውቀው አዲስ ኃይማኖት አምጥተዋል። ታላላቅ የመካ አለቆች እነዚህን ጅሎች ወደ መካ እንድንመልስ ልከውናል። የተላክነው ከአባቶቻቸውና አጎቶቻቸው ዘንድ ነው። እነዚህን እንድትመልስላቸው ይሻሉ። የጎሳ አለቆቻቸውና ህዝቦቻቸው ስለነርሱ ይበልጥ ያውቃሉ። ነውራቸውንም ይረዳሉ። የተወገዙበትንም ምክንያት ያውቃሉ።’
ኡሙ ሰለማ አሁንም ቀጠሉ…
“ዐብዱላህ ኢብኑ አቢ ረቢዓህ እና ዐምር ኢብኑል-ዓሲ ንግግራቸውን እንዳበቁ በንጉሱ ዙሪያ ያሉት ቀሳውስት ‘ንጉስ ሆይ! እውነታቸውን ነው። የራሳቸው ጎሳዎች የተሻለ ጥበቃ ይሰጧቸዋል። በምን እንዳወገዟቸውም ያውቃሉ። ለመልእክተኞቻቸው አስረክብና ወደ ህዝቦቻቸውና ሀገራቸው ይመልሷቸው አሉ።’ ይህ ንግግር ከመልእክተኞቹ ንግግር ይበልጥ ነጃሺን አናደደው። ከዚያም እንዲህ አለ። ‘በፈጣሪ እምላለሁ አሳልፌ አልሰጣቸውም። አልሞክረውም። የእኔ ጎረቤት የሆኑትን፣ ሀገሬ ላይ ያረፉትን፣ ከሌሎች ይበልጥ እኔን መርጠው የመጡትን ሰዎች ሳላማክራቸውና በመልእክተኞቹ የቀረበባቸው ክስ እውነተኛ መሆኑን ሳላረጋግጥ አሳልፌ ልሰጥ?! በፍፁም አይሆንም! ክሱ በእውነት ከሆነ ወደመጡበት እመልሳቸዋለሁ። ሐሰት ከሆነ ደግሞ እከላከልላቸዋለሁ። ሀገሬ ውስጥ እስካሉ በጥሩ ጉርብትናዬ ሥር አኖራቸዋለሁ።”
በጃዕፈርና በነጃሺይ መሀል የተደረገው ውይይት
“ከዚያም ነጃሺ የመልእክተኛውን ባልደረቦች አስጠራ። ጥሪውን እንደሰሙ ተሰባሰቡ። ‘ንጉሱ ጋር ስትቀርቡ ምን ልትሉት ነው?’ ተባባሉ። ‘ምንም ቢከሰት መልእክተኛው ያስተማሩንንና ያዘዙንን መናገር ነው ያለብን።’ ብለው ተስማሙ። ወደ ነጃሺ ሲመጡ ቀሳውስቱን ሁሉ ጠርቶ መጽሀፍቶቻቸውን ዘርግተው አገኙት። ‘ከጎሳዎቻችሁ የተለያችሁበትና ወደ አንድም ህዝብ ኃይማኖት ያልገባችሁበት ኃይማኖታችሁ ምንድን ነው?’ ብሎ ጠየቃቸው። ንጉሱን ያናገረው ጀዕፈር ኢብኑ አቢጣሊብ ነበር። እንዲህ አለው። ‘ንጉስ ሆይ! እኛ ማይማን ህዝቦች ነበርን። ጣኦታትን እናመልክ፣ በክት እንበላ፣ እናመነዝር፣ ዝምድና እንቆርጥና የጉርብትናን መብት እናጓድል ነበር። ከኛ ኃያሉ ደካማውን ይበላል።…
በዚህ ሁኔታ ላይ እያለን አላህ መልእክተኛ ላከልን። ዘሩንና እውነተኝነቱን የምናውቀውን፣ ታማኝነቱንና ጭምትነቱን የምናውቀውን ሰው ነብይ አደረገልን። ወደ አላህ ጠራን። እርሱን በብቸኝነት እንድናመልከው፣ አባቶቻችን ያመልኳቸው የነበሩ ከእንጨትና ከድንጋይ የተጠረቡ አማልክትን እንድንተው፣ እውነት እንድንናገር፣ እምነትን እንድንወጣ፣ ዝምድና እንድንቀጥል፣ ጥሩ ጎረቤቶች እንድንሆን፣ ከእርም ነገሮች እንድንታቀብና የሠዎችን ደም እንዳናፈስ አዘዘን። ከዝሙት፣ ከሐሰት ንግግር፣ የየቲምን ገንዘብ ከመብላትና ጭምት የሆኑ ሴቶችን በዝሙተኝነት ከማንቋሸሽ ከለከለን። አላህን በብቸኝነት እንድናመልከው፣ በርሱ ላይ ምንንም እንዳናጋራ አዘዘን። ሶላት እንድንሰግድ፣ ዘካ እንድንሰጥና ጾም እንድንጾም አዘዘን።”
ኡሙሰለማ አሁንም ቀጥለዋል…
“ጃዕፈር የኢስላምን መርሆች ለንጉሱ ዘረዘረና እንዲህ ሲል ቀጠለ…
‘…ከዚያም አመንነውና ይዞት የመጣውን መንገድ ተከተልን። አላህን ብቻ ማምለክ ጀመርን። በርሱ ላይም ምንንም አናጋራም። እርም የተደረገብንን ነገር ሁሉ ተውን። የተፈቀደልንን ያዝን። ከዚያም ህዝቦቻችን ድንበር አለፉብን። የስቃይ ውርጅብኝ አወረዱብን። በኃይማኖታችን ላይ ሊፈትኑን አላህን እንድንተውና ወደ ጣኦት አምልኮ እንድንመለስ ፈለጉ። ድሮ እንፈጽማቸው የነበሩ ውግዝ ነገሮችን እንድንፈጽም አስገደዱን። በደላቸው ሲበዛና ስንጨነቅ፣ በኃይማኖታችን ላይ ሲፈትኑን ወደ ሀገርህ መጣን። ከሌሎችም አንተን መረጥን። ጥበቃህንም ፈለግን። ንጉስ ሆይ! እንዳንበደልም ባንተ ወደድን!’
‘ነብያችሁ ይዞት ከመጣው መልእክት ውስጥ የምታቀርብልን ይኖርሀል?’ አለ ንጉሱ። ‘አዎን!’ አለ ጀዕፈር። ‘አንብብልኛ!’ አለ ነጃሺ። ከሱረቱል መርየም የመጀመሪያዎቹን አነበበለት። ወላሂ ነጃሺ አለቀሰ። እምባው ጺሙን አራሰው። ቀሳውስቱም ተላቀሱ። እምባቸው መፅሀፍቶቻቸውን አረጠበ።
ከዚያም ‘ይህና ሙሳ ይዞት የመጣው መልእክት ከአንድ መስኮት የሚወጡ ናቸው። ሂዱ በቃ። በፈጣሪ እምላለሁ አሳልፌ አልሰጣችሁም! አልሞክረውም!’ አለ።”
ስደተኞቹን ለመመለስ የተደረገ ዳግመኛ ሙከራ
ኡሙ ሰለማ መዘገባቸውን ቀጥለዋል…
“ሁለቱ የቁረይሽ መልእክተኞች ከቤተመንግስት ሲወጡ ዐምር ‘ወላሂ! ንጉሱን የሚያስከፋ ነውራቸውን ጠዋት እነግረዋለሁ።’ አለ። ከዐምር የተሻለ ዐብዱላህ ኢብኑ አቢ ረቢዐህ ለኛ ያዝንልን ነበር። ‘እንዲህ አታድርግ። ምንም ቢነቅፉን ዝመድና አለን።’ አለው።
ዐምር ግን ‘በአላህ እምላለሁ የመርየም ልጅ ዒሳ ባርያ ነው እንደሚሉ አስረዳለሁ።’ አለ። ከዚያም በንጋታው በጠዋት ወደ ንጉሱ ሄደና ‘ንጉስ ሆይ! እነርሱ ስለዒሳ ክፉ ንግግር ይናገራሉ! አስጠራቸውና ምን እንደሚሉ ጠይቃቸው።’ አለ።
ነጃሺ አስጠራን። ወላሂ እንዲህ አይነት ጭንቅ ወድቆብን አያውቅም። ተሰበሰብንና ተማከርን። ‘ንጉሱ ስለ ዒሳ ከጠየቀ ምን ልንል ነው!’ አልን። ከዚያም ‘ወላሂ! ምንም ይምጣ አላህና መልእክተኛው ያስተማሩንን ሁሉ እንናገራለን።’ ተባባልን። ከዚያም ወደ ንጉሱ ስንገባ ‘ስለዒሳ ምን ትላላችሁ!?’ ብሎ ጠየቀን። ጀዕፈር ኢብኑ አቢ ጣሊብ እንዲህ አለ፡- ‘ነብያችን ያስተማረንን እንላለን። ዒሳ የአላህ ባርያ፣ መልእክተኛና መንፈሱ (ሩሁ) ነው። ወደ ድንግል መርየም ያደረገው የሁን ቃሉም ነው።’
ነጃሺ እጁን ወደ መሬት ሰደደና አንዲት ዘንግ አነሳ። ከዚያም ‘ዒሳ አንተ ካልከው የዚህን ዘንግ ያህል እንኳን አያልፍም።’ አለ። ይህን ሲናገር ቀሳውስቱ አጉረመረሙ። ‘በፈጣሪ እምላለሁ! ብታጉረመርሙም ይህ ነው እውነታው።’ አለ። ከዚያም ‘እናንተ ሂዱ! በእኔ መሬት ውስጥ አማን ናችሁ! እናንተን የማረከ ይከፍላል። እናንተን የማረከ ይከፍላል! ከእናንተ አንድን ሰው አስቸግሬ ተራራ የሚያህል ወርቅ ቢኖረኝ እንኳን አላደርገውም። ስጦታቸውን አንፈልግም መልሱላቸው! በአምላኬ እምላለሁ ፈጣሪ ንግስናዬን ሲመልስልኝ ጉቦ አልበላኝም። በንግስናዬ ጉቦ ልቀበል!? አላደርገውም!’ አለ።
ሁለቱ መልእክተኞችም ተዋርደው ወጡ። ያመጡት ስጦታም ተመለሰባቸው። እኛም ከምርጡ ጠባቂያችን -ከነጃሺ ጋር- በሠላም ኖርን።”
የነጃሺ መስለም
ነጃሺ ሰለመ። በነብዩ መልእክተኝነትም አመነ። በጥመት ላይ የነበራቸውን ፅናት፣ ለስህተት ያላቸውን ጉጉት፣ በተለወጡና መሰረተ ቢስ በሆኑ እምነቶች ላይ ያላቸውን እርግጠኝነት፣ አእምሮአቸውን ለመጠቀም የማይሹ ወግ አጥባቂና ያለፈን ነገር -ስህተት ቢሆንም- እንደ ጽድቅ የሚመለከቱ ሞኞች መሆናቸውን ተመልክቶ መስለሙን ከህዝቦቹ ደብቆ ነበር።
ከአቢ ሁረይራ ተይዞ በተዘገበው ሐዲስ ላይ “ነብዩ ነጃሺ የሞተ ቀን ጥሪ አደረጉ። ለሶላት የሚሰበሰቡበት ሜዳ ላይ ወጥተው ባልደረቦቻቸውን አሰለፉ። ከዚያም አራት ተክቢራዎችን በማድረግ የሩቅ የጀናዛ ሶላት (ሶላተል-ጋኢብ) ሰገዱበት።” የሚል እናገኛለን።
ከጃቢር ኢብኑ ዐብዲላህ ተይዞ እንደተዘገበው የአላህ መልእክተኛ ነጃሺ የሞተ ቀን እንዲህ አሉ፡- “ዛሬ ቀን ደግ ሠው ሞተ። ተነሱና በጓደኛችሁ አስሀማ ላይ ስገዱበት።”
-አላህ መልካም ስራውን ይውደድለትና- ብዙ ዑለሞች የነጃሺ ሞት ከሂጅራ በኋላ ዘጠነኛው አመት ላይ በወርሀ-ረጀብ ላይ ነበር ይላሉ። መካ ከመከፈቷ ከሒጅራ በኋላ ስምንተኛው አመት ላይ ነው የሚሉም አልጠፉም።
የሐበሻ ሒጅራ አስተምህሮዎች
1. ሸረኞችና ከሀዲያን ስቃይ ካዘነቡባቸው በኋላም ሙእሚኖች በኃይማኖታቸው ላይ መፅናታቸው እውነተኝነታቸውን ይመሰክራል። የእምነታቸውን ንፅህናም ያሳያል። የነፍሳቸውን ፅዳት ያሳብቃል። የልብ እርጋታን ለኃይማኖታቸው መስዋእትነት በመክፈል ያገኙታል። የአእምሮ እረፍትን በኃይማኖት ሰበብ በሚያገኛቸው ስቃይ ይለኩታል። ቃል የተገባላቸውን -የፈጣሪያቸውን ውዴታ- ናፋቂዎች ናቸው። አካላቸውን ከሚያገኘው ቅጣት ጋር የማይወዳደር ፍቅር ከጌታቸው እንደሚያገኙ ተስፋ አላቸው። ምክንያቱም እውነተኛ ሙእሚኖችን የሚቆጣጠርና እንቅስቃሴያቸውን የሚመረምረው መንፈሳቸው ነው። እነርሱ ጋር ከመንፈሳቸው የሚቀበሉትን ትእዛዝ ለመፈፀም የሚከፍሉት መስዋእትነት ኢምንት ነው። አካላቸው ከሚፈልገው እረፍትና ጣፋጭ ህይወት መንፈሳቸው የጠየቃቸውን እንግልትና ስቃይ ያስቀድማሉ። ያኔም ሆነ ዛሬ የሙስሊሞች ዳዕዋ የሚሳካው እንዲህ አይነት ሙስሊሞች ሲፈጠሩ ነው።
2. ሒጅራን ስናስብ በቅድሚያ ልባችን ውስጥ የሚመጣው ነብዩ ለባልደረቦቻቸው ያላቸው እዝነት ነው። የእነርሱን ሰላምና ደህንነት እጅግ ይናፍቁ ነበር። እርሱ ዘንድ ማንም የማይበደል በመሆኑ ንጉሱ ጋር እንዲሄዱ አዘዟቸው። ንጉሱ ጋር እጅግ አስደሳች እረፍት አገኙ። ፊቶች ወደ ሐበሻ እንዲዞሩ ያደረጉትና ለስደተኞቹ ደህነኛ ስፍራ የመረጡት እርሳቸው ናቸው። በዚህ ሁኔታ የመጀመሪያዎቹን ሙስሊሞች ጠበቋቸው። ይህ በየዘመኑ ላሉ የሙስሊሞች መሪዎች ትምህርት ነው። ለኢስላማዊው ዳዕዋ ደህንነትና ጥበቃ አስፈላጊውን እቅድ ማዘጋጀት አለባቸው። ጥሪው የሚመሰረትበት አማን የሆነ የዳዕዋ ማእከል ያስፈልጋል። ዋናው የዳዕዋ ማእከል ላይ አደጋ ከተከሰተም ተለዋጭና ጊዜያዊ ማእከል ማዘጋጀት ያስፈልጋል። ምክንያቱም ንፁህ ምእመናን የዳዕዋ ኃብቶች ናቸው። ስለዚህ ለነርሱ አስፈላጊውን ጥበቃ ማድረግ ያስፈልጋል። አንድ ሙስሊም ከአላህ ዲን ውጪ ካሉ የምድር ሰዎች ሁሉ የተሻለ ዋጋ አለው።
3. የሐበሻው ሒጅራ ዓላማ ብዙ ነበር። ስለዚህ እነዚህን ዓላማዎች ለማሳካት መልእክተኛው የተለያዩ አቅጣጫዎችን ነበር የተከተሉት። የኢስላምን አቋሞች ከማብራራትና የቁረይሾችን ጭካኔ ከመግለፅ አንስቶ የህዝብ እምነት የሙስሊሞችን ጉዳይ በፍትህ እንዲመለከት ሀሳብ እስከማስለወጥ ድረስ ሰርተዋል። ልክ ያሁኖቹ መንግስታት ፖለቲካዊ አጀንዳዎቻቸውን ወደ ህዝብ በመበተን የብዝሀ-ህዝብን አመለካከት በነርሱ አቅጣጫ ላይ ለማድረግ እንደሚጥሩት። ስደቱ አዲስ የዳዕዋ ማእከል ለማግኘትም ጭምር የተደረገ ነው የምንለው ለዚህ ነው። ለዚህ ነው የመጀመሪያዎቹ ሶሀባዎች በጃዕፈር መሪነት የተላኩት። ከዚያም ሌሎች ሶሀቦችም ተከትለው ወደዚህ የተመሙት።
4. የነብዩ የአጎት ልጅ -ጃዕፈር-፣ አማቻቸው -ዑስማን- እና ልጃቸው ሩቀያህ ከመጀመሪያዎቹ ስደተኞች ግንባር መገኘታቸው የመሪ ቤተሰቦችና ዘመዶች የመጀመሪያዎቹ ገፈት ቀማሾች መሆን እንዳለባቸው ጥልቅ ግንዛቤ ይሰጠናል። የመሪ ቤተሰቦች ከችግርና ከስቃይ ርቀው ድሆችና ተርታ ሰዎች የሚንገላቱ ከሆነ ነብያዊውን መንገድ ያላየ ብኩን እንቅስቃሴ ነው የሚሆነው።
5. ሽሽቱ በኃይማኖት ሰበብ እስከሆነ ድረስ ሀገርን ለቆ መሰደድ ይፈቀዳል። ሀገሪቷ መካ እንኳን ብትሆን። ስደቱም ሙስሊም ወዳልሆነ ሀገር ቢሆንም። የሐበሻ ሰዎች ክርስቲያኖች ነበሩ። ዒሳ የአላህ ባሪያ ነው ብለው አያምኑም ነበር። ይህንን ያለፈው የኡሙ ሰለማ ሐዲስ ላይ ተመልክተነዋል። ይህ ስደት (ሒጅራ) ስደተኞቹን ሙሐጂሮች አስብሏቸዋል። የሐበሻዎቹ ስደተኞች ባለሁለት ሒጅራዎች (አስሀብ ሒጅረተይን) ይባላሉ። አላህ “አስ-ሳቢቁነል-አው-ወሉን” (ቀዳሚና የመጀመሪያዎች) ብሎ አወድሷቸዋል። የዚህን ንግግር ትርጉም ባወሱ ተፍሲሮች ላይ “በይዐቱር-ሪድዋን” ላይ የነበሩትም እነዚሁ ናቸው። እንግዲህ የአላህን ውዳሴ እንመልከት። ይህን ስደታቸውን አላህ አመሰገነው። ምክንያቱም ሰዎቹ ከተከበረው መስጊድ ወደ ክህደት ሀገር ተሰደዱ። ይህን ደግሞ ያደረጉት ኃይማኖታቸውን ለመጠበቅ ነው። በእነርሱና በጌታቸው መሀል ያሉ ጋሬጣዎችን ለማምለጥ። ጌታቸውን በፀጥታ ለማምለክ ነበር ምኞታቸው። አገር ጥሎ ያስኮበለላቸው ፍላጎታቸው። ይህ በዘመን የማይሻር ቋሚ ህግ ነው። ምንጊዜም ቢሆን ብክለት ሲስፋፋ፣ ሙስሊሞች ፍትህ ሲያጡ፣ እውነት በሀሰት ሲሸነፍ እና ሌላ የተሻለ ሀገር ሲያገኝ ወዲያ መሰደድ ጥሩ መንገድ ነው። ስደት እስከቂያማ ድረስ አይቋረጥም።
6. መልእክተኛው ሐበሻን የመምረጣቸው ሂደት አንድ እስትራቴጂካዊ ነጥብን ይጠቁማል። ነብዩ ያካባቢውን ሀገራት ተጨባጭ በአግባቡ ይረዳሉ። ቆሻሻውን ከንፁሁ ይለያሉ። ፍትሀዊውን ከበደለኛው ይለያሉ። ለዚህ ነው ለባልደረቦቻቸው ምቹ የስደት ስፍራ መምረጥ የቻሉት። የዳዕዋ ሰው ምን ጊዜም ቢሆን እንዲህ መሆን አለበት። ከዙሪያው እየተከሰተ ያለውን ሁሉ መረዳት አለበት። የመንግስታትንና የህዝቦችን እንቅስቃሴ መከታተል አለበት።
7. የመጀመሪያዎቹ ሙስሊሞች ጋር የነበረው የደህንነት ግንዛቤ ያስደንቃል። ለመጀመሪያው ስደት የወጡበት አወጣጥ ፍፁም ሚስጥራዊ ነበር። ይህን ያደረጉት ቁረይሾች ያሰቡትን አውቀው ቢሆን ኖሮ ሁሉን ነገር ሊያበላሹ ስለሚችሉ ነው። ስደቱም ከአስራ ስድስት ሰዎች ባልዘለለ ቁጥር መደረጉም ለዚሁ ነው። አንዳንድ ወይም ሁለት ሁለት ሆነው ሲወጡ ይህ ቁጥር ትኩረት አይስብም። በፍጥነት ለመጓዝም ያመቻል። የነበሩበት ሁኔታ እንዲህ እንዲጠነቀቁ ያስገድዳቸዋል። ምክንያቱም የስደተኞቹ ቡድን በማንኛውም ወቅት ለክትትልና ለመያዝ ሊጋለጥ ይችላል። ምናልባትም ስደቱ በሚስጥር መቀናጀቱ ቁረይሾች በጊዜ እንዳይነቁ አድርጓቸው ይሆናል። ዘግይተው ሲሰሙም በበኩላቸው ስደተኞቹን ለመመለስ የተቻላቸውን አድርገዋል። ነገር ግን ድካም ብቻ ነበር ያተረፉት። ባህሩ አካባቢ ሲደርሱ ማንንም አላገኙም። ይህ ሁኔታ ሙስሊም ጥንቁቅ መሆን እንዳለበት ያስተምረናል። በዳዕዋ ውስጥ የሚያደርጋቸውን እንቅስቃሴዎች ሁሉ ይፋዊ ማድረግ የለበትም። ምክንያቱም የደህንነት ግንዛቤው ባነሰ ቁጥር ዳዕዋው ለአደጋ ይጋለጣል።
8. ቁረይሾች ሙስሊሞች ወደ ሐበሻ መሰደዳቸውን አልወደዱም። ምክንያቱም ስደቱ አሁን ባይሆንም የወደፊት ጥቅማቸውን ይጋፋል። ምናልባት ወደፊት የስደተኞቹ ቁጥር ይጨምራል። ከዚያም ኃይላቸው ይበረታና ለቁረይሾች አደገኛ ይሆናሉ። ስለዚህ ቁረይሾቹ ስደተኞቹን ለመመለስ የተቻላቸውን ማድረግ ጀመሩ። ሙሐጂሮቹን ተከተሏቸው። አልደረሱባቸውም። ከዚያም ለነጃሺና ለአማካሪዎቹ የተደረገው የስጦታ ጋጋታ መካ ውስጥ ሆነው ያወጡት የስጦታ አሰጣጥ ዘዴያቸው ያስደንቃል። ከስጦታው ጋር የተያያዘው ንግግርም ረቂቅ ነው። የአምባሳደር አመራረጣቸውም ልዩ ነው። ምክንያቱም ዐምር ኢብኑል-ዓስ የነጃሺ ወዳጅ ነበር። ይህ ሁሉ ቁረይሾች ነገሮችን የሚያዩበት መንገድ እጅግ ረቂቅ እንደነበር ያሳያል።
9. ጠላቶቻችንን አሳንሰን መመልከት እንደማይገባ ከዚህ መማር አለብን። እቅዶቻቸውንም ተኝተን መጠበቅ የለብንም። እውነተኛ ግዝፈታቸውን ልንሰጣቸው ይገባናል። እንቅስቃሴያቸውንም ልንቆጣጠር ይገባል። ኃይላቸውን መጋፈጥ የምንችለው እንዲህ ስንሆን ብቻ ነው።
10. ቁረይሾች ያላቸውን ዘዴና ኃይል ተጠቅመው ስደተኞቹ ነጃሺ ፊት እንዳይናገሩ ለማድረግ ሞክረዋል። ነገር ግን አልቻሉም። ምክንያቱም የነጃሺ ፍትሀዊ ስብእና ተከሳሽን ሳያዳምጥ መፍረድ አልፈቀደም። ስለዚህ ሙስሊሞች ጉዳያቸውን የማቅረብና እራቸውን የመግለፅ እድል አገኙ። ከዚያም ጃዕፈር በሚያስደንቅ ጥበብ ተጠቀመበት። እኛም በምናገኘው አጋጣሚ ሁሉ ዲናችንን የማንፀባረቅና መርሆቹን የመግለፅ አቅማችንን ማሳደግ አለብን።
11. ሶሐቦቹ ነጃሺ ሲያስጠራቸው ምንድን ነው ያደረጉት? ተሰበሰቡና ሁኔታዎችን አጠኑ። ከዚያም ተማክረው ተመሳሳይ አቋም ላይ ደረሱ። ሁሌም ሙስሊሞች እንዲህ መሆን አለባቸው። በመሀላቸው መመካከር (ሹራ) ሊኖራቸው ይገባል። በሹራ የሚሰራ ነገር ሁሉ የተሻለ ስኬት ያመጣል። ውሳኔው የብዙህ ሐሳቦች ጭማቂ ይሆናል።
12. ከሒጅራ ክስተት የነብዩን የተርቢያ (ስልጠና) ንቃት እንመለከታለን። ወጣቱን ጃዕፈርን የሒጅራ አሚር ማድረጋቸው ይህን ያሳያል። ከዚያ ሙሐጂሮቹ ጀዕፈርን የነርሱ ቃል አቀባይ አደረጉት። ከብስል የቁረይሽ ልዑኮች ጋር እንዲፋጠጥ ሾሙት። ጀዕፈር ለዚህ ኃላፊነት እንዲታጭ ያደረጉት ነጥቦች አሉ። ከነዚህ መሀል፡-
- ጀዕፈር ለነብዩ ቅርብ ነው። አንድ ቤት ውስጥ ለረጅም ጊዜያት ኖረዋል። የዳዕዋውን መሪ -ነብዩን- ከማንም በላይ ያውቃቸዋል።
- ነጃሺ ፊት የሚደረገው ፍጥጫ ፍፁም የቋንቋ ጥበብና የንግግር ችሎታ ይጠይቃል። በኒ ሀሺሞች ደግሞ ከቁረይሾች መሀል በዚህ ረገድ ምርጥ የሚባሉ ነበሩ። ጀዕፈር ደግሞ የነርሱ አባል ነው።
- ጀዕፈር የነብዩ የአጎት ልጅ መሆኑ ስለሚሰማው ነገር እውነተኝነት እንዳይጠረጠርና የንጉሱ ልብም እንዲረጋጋ ያደርጋል።
- ከነብዩ የተቀሰመው የጀዕፈር ስብእናና እርሳቸውን የሚመስለው ውብ ተክለ-ሰውነት ተመራጭ አድርጎታል። መልእክተኛው “ስብእናዬንና ተክለ-ሰውነቴን ተመሳሰልክ።” ብለውታል።
- ስለዚህ ነጃሺ ፊት የሚቆመው አምባሳደር ከርሱ በኋላ ለሚመጡ አምባሳደሮች በሙሉ ተምሳሌት መሆን አለበት። ለኢስላም ያለው ወገንተኝነት፣ የንግግር ችሎታው፣ እውቀቱ፣ መልካም ስብእናው፣ ትእግስቱ፣ ጀግንነቱ፣ ጥበቡ፣ ዘደኝነቱና የሚያምረው ተክለሰውነቱ ምርጥ የሙስሊሞች አምባሳደር ያደርጉታል።
13. ዐምር ኢብኑል-ዓሲ ከብልህነቱና ከአስተዋይነቱ ጋር ለነብዩና ሶሐቦቻቸው ታላቅ ጥላቻ ከነበራቸው ሰዎች መሀል ነበር። ጀዕፈር ወደ ነጃሺ ከመምጣቱና ከመናገሩ በፊት የቻለውን ማስረጃ በሙሉ ነጃሺንና አማካሪዎቹን ሞልቷቸው ነበር። በተለይም ስለተከታዮቹ ነገሮች አውርቶ ነበር።
- የነብዩ ሙሀመድ ጥሪ መካ ውስጥ የእርስበርስ ፍጅትን ሊያስከትል የሚችል ጥላቻ እያመጣ መሆኑን አስረድቷል። በተለይም ቁረይሾችን ወክሎ እንደመጣ ልዑክ ይህ ንግግሩ ነጃሺ ጋር ታማኝ ነው። በተጨማሪም የነጃሺ ወዳጅ ነው።
- የነብዩ ሙሐመድ ተከታዮች አደገኛነት ልክ መካን እንዳንቀጠቀጡ የነጃሺንም ንግስና ሊያንቀጠቅጡ እንደሚችሉ ነግሮታል። በተለይም ይህን ሀሳብ ቁረይሾች ለነጃሺ ካላቸው ፍቅርና ውዴታ ጋር አያይዞ አቀረበው። እንዲህ አለው፡- “አንተ ለኛ ባለውለታችን ነህ። ለቤተሰቦቻችን መልካም ትውላለህ። ነጋዴዎቻችን አንተ ጋር ጥበቃና ሰላም ያገኛሉ።” ስለዚህ ለዚህ ውለታው ምላሽ ቁረይሾች ፈተና ሊያመጡበት የሚሹትን የሙሐመድን ተከታዮች እንዲጠነቀቅ እንሚመክሩት ገለፀ።
- ከሁሉም አደገኛው ደግሞ ስደተኞቹ ከነጃሺ እምነት ያፈነገጡ መሆናቸው ነው። “የመርየም ልጅ ዒሳ አምላክ መሆኑን አያምኑም። ስለዚህ እነርሱ በጎሳዎቻቸው እምነት ላይ እንዳልሆኑ ሁሉ ባንተም እምነት ላይ አይደሉም።” አዲስ የመጡ ፈተና ቀስቃሾች ናቸው ማለቱ ነው።
- የንጉሱን ክብር ዝቅ ማድረጋቸው ሌላው ነውር ነው። ሁሉም ሰው ሲሰግድለት እነርሱ ግን አንገታቸውን እንኳን አያጥፉለትም። እንዲህ አይነት ንቀት እያላቸው እነርሱን ማስጠጋት ለራስህም ስጋት አለው። ብሎ አስረዳ፤ ዐምር። እነዚህን የቁረይሽ መልእክተኛን ትችቶች ማፈራረስ የጃዕፈር ጫንቃ ላይ የወደቀ ኃላፊነት ነበር።
14. የጃዕፈር ምላሽ የመጨረሻውን የብስለት ደረጃ የደረሰ ረቂቅ ነበር። ጥልቅ የፖለቲካ እውቀትንም ያሳየ ነበር። የእምነት ጥንካሬን፣ የዳዕዋ ጥበብንና የዲፕሎማሲ እውቀትንም ያካትታል። እንዲህ ነበር ያደረገው፡-
- የጃሒሊያን ነውሮች ገለፀ። አዳማጩን በሚያስፀይፍ ሁኔታ አቀረበው። ንጉሱ ዘንድ ያለውን የቁረይሾችን ስዕል ማበላሸት ነበር አላማው። ትኩረት ያደረገባቸው ብክለቶችም በነብያት እንጂ የማይገፈፉ እድፎች ናቸው።
- በቆሻሻ በተሞላው ማህበረሰብ ውስጥ ደግሞ የነብዩን አንፀባራቂ ስብእና አስቃኘ። ከጉድለት ሁሉ የጠሩ ንፁህና ልዩ ፍጡር መሆናቸውን አሳወቀ። በዘራቸው፣ በእውነተኝነታቸው፣ በታማኝነታቸውና በጭምታቸው የታወቁ መሆናቸውን ተናገረ። ለነብይነት የሚያሳጩ ባህሪያት በሙሉ በነብዩ ስብዕና ላይ እንዳለ አስረዳ።
- ጀዕፈር የኢስላምን ውበት እና ከሌሎች ነብያት ጥሪ ጋር ያለውን የመርህ ትስስር ገለፀ። ጣኦትን መተው፣ እውነት መናገር፣ እምነት መወጣት፣ ዝምድናን መቀጠል፣ መልካም ጉርብትና፣ የሰውን ክብርና ደም መጠበቅ፣ ሶላት መስገድ፣ ዘካን መስጠት… የሁሉም ነብያት ጥሪ የሚሽከረከርባቸው ጉዳዮች ናቸው። ነጃሺና አማካሪዎቹ ክርስትና ውስጥ የኖሩ መሆናቸው ይህን የነብያት ጥሪ እንዲገነዘቡ ያደርጋቸዋል።
- ጣኦታትን አናመልክም በማለታቸው ብቻ በቁረይሾች የደረሰባቸውን ግፍ በመግለፅ አዋረዳቸው።
- ነጃሺን አሞገሰው። ፍትሀዊ እንደሆነና እርሱ ዘንድ ማንም እንማይበደል ተናገረ።
- ከሌሎች እርሱን እንደምሽግ እንደመረጡት፣ ከበደልና ስቃይ ለመዳን ወደርሱ እንደሸሹ በመግለፅ የዐምርና የባልደረባውን ንግግር አፈራረሰው። የነጃሺንና የአማካሪዎቹን ልብ ማረከ። አእምሮአቸውንም ተቆጣጠረ።
- ነጃሺ በመልእክተኛው ላይ ከወረደው መሀል አንብብልኝ ሲለውም ሱረቱል-መርየምን መረጠ። ባማረ ሁኔታም አነበበው። ነጃሺና አማካሪዎቹ እስከሚያለቅሱ ድረስ ማረካቸው። በተለይም ይህን ሱራ መምረጡ የርሱን ጥበበኝነትን ያመለክታል። ይህ ሱራ ስለ መርየምና ስለዒሳ በስፋት ይዳስሳልና።
- ስለ ዒሳ ባህሪ በተጠየቀ ጊዜ የተናገረውም አስደናቂ ነው። ዒሳን አምላክ እንደማያደርጉት ገለፀ። ነገር ግን መርየምን ከሚያንቋሽሹ ሀሰተኞችም እንዳልሆኑ አብራራ። ዒሳ የአላህ መልእክተኛውና ባሪያው ነው። ወደ ብፀእት መርየም ያኖረው የሁን ቃሉና መንፈሱ እንደሆነ አብራራ። እርሷም ንፁህ ሴት እንደሆነች ተናገረ። ከዚያም ነጃሺ ከዚህ ንግግር አንዲትንም መጨመር አልቻለም። የአንዲት ዘንግ ያህል እንኳን ዒሳ ከዚህ እንደማያልፍ መሰከረ።
- ለነጃሺ አይሰግዱም። አላህን በርሱ ሊለውጡ አይሹም። ስግደት ለአላህ እንጂ ለማንም አይገባም። ነገር ግን ንጉሱን አይንቁትም። ያከብሩታል። ልክ ለነብያቸው የሚሰጡትን ሰላምታ ለርሱ ይሰጡታል። የጀነት ሰዎች እርስ በራሳቸው የሚሰጣጡትን ሰላምታ ይሰጡታል።
- በመጨረሻ ነጃሺ የስደተኞቹን እውነተኝነት መሰከረ። ንፅህናቸውንም አመነ። የሙሳና የዒሳ አይነት መልእክት ከጂብሪል (ናሙስ) የተቀበለውን መልእክተኛ ለማገልገልም ቆረጠ። የርሳቸውን ባልደረቦች በመንከባከብ ወደ አላህ ለመቃረብ ወሰነ። ከቁረይሾች ጋር ያለው ግንኙነት ቢበላሽም እንደማይጎዳና ከነርሱ ንግድ የሚያገኘው ገንዘብ ቢቀርም ምንም እንደማይሆን ለዐምር ነገረው።
- በዚህ ጥበብና ዕውቀት በፖለቲካ፣ በዲፕሎማሲና በእምነት መድረክ ላይ ቁረይሾች ተሸነፉ።
15. የጀዕፈርና ባልደረቦቹ ገድል ለኢስላም አስተምህሮ ተግባራዊ ማሳያ ናቸው። “ሰዎችን በማስቆጣት የአላህን ውዴታ የፈለገ ከሰዎች ተንኮል አላህ ይገላግለዋል። አላህን በማስቆጣት የሰዎችን ውዴታ የፈለገ ሰው ደግሞ አላህ ለሰዎች አሳልፎ ይሰጠዋል።” የሚለውን ነብያዊ አስተምህሮ በነዚህ ሶሐቦች ተግባር ላይ ተገልፆ እናገኛለን። ክርስቲያኖቹን ሊያስከፋ የሚችል ቢሆንም የአላህን ውዴታ ፈልገው በዒሳ ላይ ያላቸውን እምነት በግልፅ አስቀመጡ። በክርስቲያኖቹ ጥበቃ ሥር ቢሆኑም በዚህ ጊዜ አላህ የነጃሺን ልብ አገራላቸው። ውጤቱ ላይ ነጃሺ እውነተኛ ቃሉን ተናገረ። ከተበረዘው የክርስትና ጥሪ የተቃረነ ቢሆንም የነብዩ ሙሐመድ ጥሪ ሐቀኛ መሆኑን መሰከረ። የንግስናው እግር ይህ እምነት ላይ የቆመ ቢሆንም ነጃሺ እውነቱን መደበቅ አልቻለም። ኋላም ፅንፈኞች አምፀውበት ወደ ትግል አምርቷል።
16. የዐምር ቢን አልዓሲ (አንዱ የቁረይሽ ልዑክ) እስልምና የጀመረው ሐበሻ በመጣበት ነው። ይህም የሐበሻ ስደት ካመጣቸው ትላልቅ ትርፎች መሀል የሚቆጠር ነው። ሙሐጂሮቹ ስደት ላይ በቆዩበት ጊዜ ካስገኟቸው ውጤቶች አንዱ ነው። አንዳንድ ዘገባዎች እንደሚሉት ዐምር ኢብኑል-ዓሲ በነጃሺ እጅ እስልምናን ተቀብሏል። ይህ እውነት ከሆነ ዐምር በታቢዕ (ነብዩን ባላገኘ ሰው) እጅ የሠለመ ብቸኛው ሶሐባ ይሆናል ማለት ነው። ይህን ዘገባ ኢማም ኢብኑ ሐጀር ጠቅሰውታል። በጃዕፈር እጅ እንሠለመ የሚጠቁሙ ሌሎች ዘገባዎች እንዳሉም አል-ዙርቃኒ ጠቅሰዋል።
17. ነብዩ ኡሙ ሐቢባን ያገቡበት አጋጣሚም ከዚሁ ስደት ጋር ይቆራኛል። ይህ ጋብቻ ባሏ ሞቶባት እንኳን በእምነቷ በፀናች ሴት ላይ የሚፈጥረው የመንፈስ መነቃቃት ቀላል አይደለም። የጋብቻ ውሉ የተጠናቀቀው ኡሙ ሐቢባ ሐበሻ ውስጥ እያሉ ነው።
አቡ ዳዉድ በትክክኛ (ሶሒሕ) ሰነዳቸው እንደዘገቡት ኡሙ ሐቢባ የዑበይዲላህ ኢብኑ ጀሕሽ ባለቤት ነበረች። ባሏ ሞተባት። ከዚያም ነጃሺ አራት ሺህ ዲርሀም እንደመህር በመክፈል ለነብዩ ዳራቸው። ከሹረህቢል ኢብኑ ሐሰናህ ጋር አብሮ ወደርሳቸው ላካት።
ይህን ሐዲስ ከልቡ የተመለከተ ሰው ነብዩ የሙሐጂሮቹን ሁኔታ በጥሞና ይከታተሉ እንደነበር ይገነዘባል። በችግር ጊዜያቸውም ላይ ሀዘናቸውን ይጋሩ እንደነበር ያውቃል። ትእግስተኞቻቸውን ያፅናናሉ። ፅናታቸውንም ያደንቃሉ። በተለይም ወደ ሐበሻ የተሰደዱትን ሴቶች ታሪክ ስንከታተል ኡሙ ሐቢባ የነብዩን ድጋፍ ያገኘች ብቸኛ ሴት አትሆንብንም። ወደ ሐበሻ ተሰዳ የነበረችው ሰውዳ ከሐበሻ ወደ መካ ከባሏ ጋር ነበር የተመለሰችው። መካ እንደመጡ ባለቤቷ ሰክራን ቢን ዐምር ሞተ። ከዚያም ነብዩ ሊያጯት ፈለጉ። “በእኔ ጉዳይ ላይ እርሶን ሾሜያለሁ!” አለቻቸው። “ከጎሳሽ አንዱን ሰው እንዲድርሽ እዘዢውና ይዳርሽ።” አሏት። ሐጢብ ቢን ዐምር ቢን ዐብዱሽ-ሸምስ ቢን ዐብዱወድ-ድን ወከለችውና ዳራት። ሰውዳህ ነብዩ ከኸዲጃ በኋላ ያገቧት የመጀመሪያዋ ሴት ሆነች።
ዘገባዎች የነብዩ ባለቤቶች ከአንድ በላይ የሆነበትን ጥበብ በጥቅሉ ያሳያሉ። በሌላ በኩል ደግሞ በእንዲህ ባለ ጊዜ ለሴቶች ሊሰጥ የሚገባውን ከፍተኛ ትኩረት ይገልጣሉ። ሌሎች ምክንያቶችንም መደርደር ይቻላል። ለምሳሌ ነብዩ ኡሙ ሐቢባን ሲያገቡ የበኒ ኡመያዎችን ጥላትነት ለመቀነስም ነበር። በተለይም የእነርሱ መሪ የነበረውን የአባቷን የአቡ ሱፍያንን ጥላቻ ለማብረድ ነው።
18. ነብዩ ወደ ሐበሻ ሊሰደዱ ያስቡ ነበር ይባላል። ታዲያ ምን አገዳቸው? አንዳንድ ተመራማሪዎች የሚከተሉትን አስተያየቶች ይሰጣሉ።
- ነብዩ እንዲሰደዱ የሚታዘዙበትን ቦታ በህልም አይተዋል። የስደት ቦታቸው በተምር ዛፎች የተሞላች ናት።
- የዐረቢያ ደሴት ለዳዕዋ ማዕከልነት የታጨበት ምክንያት ሠፊ ነው። ስለዚህ ዋናው የዳዕዋ ማእከል መካ ከዚያም መዲና እንደሆኑ ታስቧል።
- የሐበሻ ጆግራፊያዊ አቀማመጥ ዳዕዋው እንዳይሰራጭ ገደብ ሊሆን ይችላል።
- ይህ የአዲሱ ነብይ ጥሪ ጥገኛ ሆኖ ከኖረበት የክርስትያኑ አየር ጋር እድገቱን ያገኛል ተብሎ አይታመንም። በተለይም የዘመኑ ክርስቲያኖች መሪ የነበረችው ታላቋ ሮማ እስልምና ሐበሻ ውስጥ እንዲያብብ ትፈቅዳለች ተብሎ አይታሰብም።
*****